
የወያኔ ጉጅሌ ራሱ ከሳሽ፣ ፖሊስና ዳኛ ሆኖ በሚገዛት ሀገራችን ውስጥ የሚያካሂደው ግፍ አንድ ህዝብ ሊሸከመው ለሚችለው በላይ ሆኗል።
የወያኔ ሹማምንትና በዘር ለዝርፊያ የተሰማራው ድርጅታቸው በቅርቡ ደግሞ ስዘርፍ አያችሁኝ በሚል ቁጣ ከአንደበታቸው በላይ ምንም ባልታጠቁ የኦሮሞ ተማሪዎች ላይ ከአካሄደው ጅምላ ጭፍጨፋ አልፎ ግለሰብ ተማሪዎችን በማሳደድ ሰቆቃ መፈጸሙን ቀጥሎበታል። በዚህ ሰአት በርካታ ተማሪዎች በታወቁና ባልታወቁ እስር ቤቶች ታጉረዋል። ብዙዎቹ ከትምህርት ገበታ ካላንዳች ጥያቄ ተባረዋል እየተባረሩም ይገኛሉ።
ከወያኔ ግፎች ሁሉ በእጅጉ የሚዘገንነው ሌሎችን በመወንጀል ማሰቃየትና መግደል በፈለገ ቁጥር ራሱ ወንጀል ከፈጸመ በኋላ ወንጀሉን በሌሎች ላይ ለማመኻኘትና ለመቅጣት የሚጠቀሙበት የሃሳብ ዘዴ ነው።
በአለምያ ዩኒቨርስቲ ተማሪዎች በተሰበሰቡበት አዳራሽ ውስጥ የደህንነት አባሎች ቦንብ አፈንድተው ጉዳት ካደረሱ በኋላ የሚፈልጓቸውን ወጣቶች ቦንብ ሲያፈነዱና ሲጠምዱ ያዝናቸው በማለት ከዚህ በፊት በዊክሊክ መረጃ እንደተለቀቀው የተለመደ በሰው ልጆች ላይ ሰቆቃ ይፈጽማሉ። ሌላው ቀርቶ ቦምብ አፈነዱ ተብለው የተከሰሱት ተማሪዎች በገዛ ጓደኞቻቸው ላይ ቦምብን የሚወረውሩበት ምክንያት የላቸውም።